የሪል ስቴት ገበያው እንዲሰክን አድርጓል!

 የሪል ስቴት ገበያው እንዲሰክን አድርጓል!


#Ethiopia  | የአዲስ አበባ ከተማ ሪል ስቴት ገበያ በዋጋ  ደረጃ  ለመስከኑ  የኦቪድ ግሩፕ አስተዋፅዎ ቀላል አይደለም ።  ኦቪድ ግሩፕ በሪል ስቴት ልማት ክንፉ ፣ የገነባቸው ቤቶችን በብዛት ለገበያ ማቅረቡ የሪል ስቴት ገበያው እንዲሰክን አድርጓል - ወይም ሰብሯል ።


ቀደም ባሉት ወራት  በዋጋ ሽቅብ ይጎን የነበረው የሪል ስቴት ገበያ የዋጋ ቅናሽ እየታየበት ነው - ዋጋውን ጣሪያ የሰቀሉ ጭራሽኑ ጠያቂ አጥተዋል ። 


ግዙፉ የሪል ስቴት ዘርፍ ዘገር ነቅናቂ ሆኖ  የቀረበው ኦቪድ - በታሪክ ተመዝግቧል  ...... ብራቮ ዮናስ ታደሰ !


በአዲስ አበባ ከተማ የሪል ስቴት የካሬ ሜትር ዋጋ ወቅታዊ ነፀብራቅ ምን መልክ ይዟል ተብሎ ቢታይ -   የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳዳር ባስጠናው ጥናት የአንድ ካሬ ሜትር የሪል ስቴት መገንቢያ ዋጋ ከ 30,000 ብር እስከ 40,000 ብር - አለፍ ብሎም እስከ 50,000 ብር ነው ። 


ነገር ግን ይህንን ዋጋ ብዙዎቹ የሪልስቴት አልሚዎች  በፍፁም አይቀበሉትም ። ይልቁኑ እንደየ ሪልስቴት ግንባታው ደረጃ የሚለያይ ቢሆንም በአልሚዎች  ጥናት የሪል ስቴት የግንባታ ዋጋ በካሬ ሜትር ከ 63,000 ብር እስከ 70,000 ብር ይደርሳል።


የሪል ስቴት መገንቢያ ቦታ በሁለት መንገድ ይገኛል ። አንድም ከአስተዳደሩ ሁለትም ከግለሰቦች በግዥ ። ከግለሰቦች በግዥ የሚገኘው ውድ እንደመሆኑ በግንባታው ላይ የመሬት ዋጋ ፣ የሠራተኛ እና የመሳሰሉ ወጪዎች ሲጨመሩበት ዋጋውን ማናሩ አይቀርም ።


ኦቪድ ግሩፕ ገበያውን ከመቀላቀሉ በፊት አብዛኛዎቹ አልሚዎች ለገበያ ያቀረቡትን ሪል ስቴት በካሬ ከ 80,000 ብር እስከ 120,000 ብር ይጠሩ ነበር - በውጭ ምንዛሪ ደግሞ በካሬ ሜትር ከ 3,000 እስከ 4,000 ዶላር ድረስ ይጠራሉ - ከዚህም በላይ ዋጋ የሚጠራላቸው ቅንጡ ሪልስቴቶች እዚህም እዚያም እንዳሉ አሉ! 


በአሁኑ ገበያ ግን በካሬ ሜትር  70,000 ብር እና ዙሪያውን ፣ በውጭ ምንዛሪም 2,000 እና ዙሪያውን እየተጠራ ይገኛል ። ከዚህ ባለፈም ከ10 እስከ  20 በመቶ ቅናሽ ማማለያ እየተሰጠ ነው ። 


በዚህ መሀል ማን ሰንጥቆ መጣ !? ለሦስት አስርት ከግንባታ ተገልሎ የቆየው የፌደራል ቤቶች ኮርፖሬሽን በለውጡ  ዳግም አንሰራራ - ረሻድ ከማል የሚባል ዶዘር መጣለት - ፌቤኮ ተገማች ባልሆነ መንገድ በዋና ዋና ግንባር ቦታዎች ሁነኛ ህንፃዎችን ገንብቶ ባልተጠበቀ ዋጋ ቤቶችን ገንብቶ ለገበያ ሲያቀርብ - ገበያው ከኢኮኖሚ ማንሰራሪያ ባሻገር ለብዙሃኑ ሃብት ሆነ ...


ግን ግን የግልና መንግስት አጋርነት ( PPP ) ከመንግስት በ 70/30 ቀመር መሬት የወሰዱ ሪል ስቴት አልሚዎች በስንት ብር ቢሸጡት ያዋጣቸው ይሆን !? 


በ70 ሽህ ? መንግስት ከተገነባው ሪል ስቴት ድርሻውን ሲወስድ አልሚዎቹ የመገንቢያ ዋጋውን እንዴት አብቃቅተው አትራፊ ይሆኑ ይሆን - ልናይ ኋላ! 


በልዩ ሁኔታ የሚታይ ቢሆንም  የፐርፐዝ ብላክ ዋጋ ሳያስደምም የሚቀር አይደለም - የፐርፐዝ ብላክ ነገር እስካሁን መጨረሻው ባይለይም አምስት ቢሊየን ብር ቦታ ገዝቶ ፤ በ 60 ቢሊዮን ብር 113 ወለል ህንፃ ከነ አጀቡ ገንብቶ -  ከአክሲዮን ድርሻ ጋር ፣ መቶ ካሬ ሜትር ቤት በ 1.5 ሚሊዮን ብር ፤ ቆየት ብሎም በ3.5 ሚሊዮን ብር ሂሳብ ( በካሬ ሜትር 15,000 ብር እና 35,000 ብር መሆኑ ነው  ) መዋዋሉ ከትርፋማነት ቀመር ውጭ ነው ።


የአዲስ አበባ ከተማ ሪል ስቴት ዘርፍ ለመኖሪያ ፈላጊው ጥሩ አማራጭ ገበያ እንዲሆን ካስፈለገ የመሬት አቅርቦት ፣ የፋይናንስ አማራጭ ፣ የሸማች መብት ጥበቃ ወሳኝነት አላቸው - በአገሪቱ ውስጥ የሚገኙ ቢሊየነሮች የገቡበት ዘርፍ መሆኑ ልብ ይሏል - የዚያኑ ያህልም የተካኑ ባለካልኩሌተሮችም ዘርፉን ተቀላቅለዋልና መፍዘዝ ጥሩ አይደለም !


ውድነህ ዘነበ

Comments

Popular Posts